Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Saturday, August 27, 2016

ዶ/ር ሼክስፒር ፈይሳ ብራዚል ድረስ ሄደው ለአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ጥብቅና እንደሚቆሙ ቃል ገቡ

አስደሳች ዜና – ዶ/ር ሼክስፒር ፈይሳ ብራዚል ድረስ ሄደው ለአትሌት ፈይሳ ሌሊሳ ጥብቅና እንደሚቆሙ ቃል ገቡ
ጴጥሮስ አሸናፊ እንደዘገበው
ጀግናው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ በሪዮ ኦሎምፒክ በማራቶን ታላቅ ድል ካስመዘገበና ህወሃትና ታማኝ ጦሩ የሆነው አጋዚ በኢትዮጵያውያን በተለይም በታላላቆቹ የኦሮሞና አማራ ብሔረሰቦች ላይ የሚያካሂዱትን የዘር ማጥፋት፣ የመግደል፣ የማሰር፣ የመጨፍጨፍ፣ የማዋከብና የማሳድድ ተግባርን በአለም አቀፍ መድረክ በቢሊዮን ለሚቆጠሩ የአለማችን ህዝቦች በኦሎምፒክ አደባባይ ከፍ አድርጎ በማሳየቱ የሃገራችን ሕዝቦች፣ የሃገራችን ወዳጆችንና በአምባገነኖች የሚረገጡና የሚጨቆኑ ጥቁር አፍሪካውያንን ያኮራ ታሪካዊ ጀግንነትን በመፈፀሙ ገድሉ በአለም አቀፍ ደረጃ በአራቱም መዐዘን በመገናኛ ብዙሃን እየተነገረለት ይገኛል።
የወንዶች ማራቶን ውድድር በታላቁ የኦሎምፒክ መድረክ የመዝጊያ ቀን የሚካሄድ እንደመሆኑና ከውድድሩ መጠናቀቅ በኋላ የተሳታፊ ሃገሮች ተወዳዳሪዎችና የልዑካን ቡድን አባላትም ወደየሃገራቸው ለመመለስ የሚዘጋጁበት ጊዜ በመሆኑ የኢትዮጵያን ኦሎምፒክ ቡድን የሚመሩት የህወሃት አባላት ጀግናውን አትሌት እንዳያዋከቡትና ወደ ሃገር ቤት እንዲመለስ ጫናና ግፊት እንዳያደርጉበት ኢትዮጵያውያንና አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተከራካሪ ተቋማት አፋጣኝ እንቅስቃሴ እንዲጀምሩ በመላው አለም የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በመጎትጎት ላይ ይገኛሉ።
የጉዳዪን አሳሳቢነትና የሕዝባችንን ስጋት በመረዳት አሁን ማምሻውን በአጭር ጊዜ የተዋቀረ አለም አቀፍ ግብረ ሃይል አስቸኳይ ውይይት በማድረግ ላይ ሲሆን በቀጣይ ቀናትም ያለውን የሙያተኞች ስብስብ በማስፋት ለጀግናው አትሌት የአለንልህ ጥሪውን ለማሰማት የሚቻለውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን በታላቅ ደስታ ይገልፃል።
እስካሁን መቀመጫቸውን በአሜሪካን ሃገር ሲያትል ዋሺንግተን ያደረጉት የሕግ ባለሙያ ዶ/ር ሼክስፒር ፈይሳ እንደ አጋጣሚም ፓስፖርታቸው ላይ የብራዚል ቪዛ ስላላቸው በራሳቸው ወጪ ወደ ሪዮ በመሄድ ለጀግናው አትሌት በነፃ ጠበቃው ለመሆን ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል ሌሎችም የሕግ ባለሙያዎች እንዲቀላቀሏቸው ጠይቀዋል።
የህወሃት መንግስት በነገው ዕለትና በመጪዎቹ ቀናት ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮችን ወደ ብራዚል እንደሚልክና ከብራዚል መንግሥት ተወካዮችም ጋር ግንኙነቶችን እንደጀመረ ምንጮች እየጠቆሙ ቢሆንም የብራዚል መንግሥት ሰላማዊ ዜጎችን በአደባባይ በጥይት ለሚገድለው ህወሃት አዎንታዊ መልስ ይሰጣል ተብሎ አይገመትም።
የህወሃት መንግሥት ከሁለት አመት በፊት የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሆነውን የመንገደኞች አውሮፕላን በመጥለፍና ጄኔቫ ስዊዘርላንድ በማሳረፍ የሥርአቱን ገመና ያጋለጠውን ረዳት አብራሪ ኃይለመድኅን አበራን ከስዊዘርላንድ ወደ ኢትዮጵያ በማስመለስ ለማሰቃየትና ለመግደል አድካሚ የዲፕሎማሲ ጥረት ቢያደርግም በስዊዘርላንድ መንግሥት ጥያቄው በተደጋጋሚ ውድቅ እንደተደረገበትና የስዊዘርላንድም ከፍተኛው ፍርድ ቤት ኃይለመድኅንን በነፃ እንዳሰናበተው የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው።

No comments:

Post a Comment

wanted officials