Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, November 23, 2016

በአትላንታ ሰዐሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል መቋሚያ ያማዝዙ ጥያቄዎች

በአትላንታ ሰዐሊተ ምህረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል የነበረን ሰላም ደፍርሶ በቤተመቅደስ ውስጥ በታቦቱ ፊት ለፊት ምእመናኑን መቋሚያ ሲያማዝዙ በዓይናችን ተመለክተናል። ይህንን የተመለከተ አንድ ኦርቶዶክሳዊ ግለሰብ ይህ ለምን ሆነ? እየተካሄደ ያለው ነገር ምንድነው? እንዴት በዚህ ወቅት ሆነ? ይህንን የሚደርገው ሃይልስ ማነው? እንዴት ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚል ጥያቄዎችን ያጭራል።
abune-yakob
1፦ስርዓተ ቤተክርስቲያን እና የቤተክርስቲያና ህገ ደንብ ስለተጣሰ ነው።የጣሰው  አካል ምእመናን ህግ አክብረው እንዲያስከብሩ መርጦ ሃላፊነት የተሰጣቸው የተወሰኑ የቦርድ አባላት እና አስተዳዳሪው ካህን ናቸው። ከሞላ በጎደል መቋሚያ አማዛዡ የቦርድ ክፍል የሚከተሉትን ህጸጾች ፈጽሟል።
ሀ-መጥራት የነበረበት ሁለት አጠቃላይ ስብሰባ እና አንድ የበጀት ማጽደቂያ ስብሰባ አልጠራም።
ለ-የቤተክርስቲያንን ክብር በሚጋፋ መልኩ በመንፈሳዊ አስተዳደር ጣልቃ እየገባ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ያዕቆብ የእለት ከእለት ተግባራቸውን እንዳይፈጽሙ የማስፈራሪያ ደብዳቤዎች በመላክ አሉታዊ ተጽእኖ አድርጓል።
ሐ-ህገ ደንባችን በምእራፍ 3 አንቀጽ 3 ላይ ቤተክርስቲያኗን በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ ማኅበረ ምእመናን  የመጨረሻው ወሳኝ አካል ነው የሚለው አንቀጽ ጥሰው  ከ300 በላይ ምእመናን የብጹእ አቡነ ያዕቆብ አገልግሎትና ቡራኬ እንፈልጋለን የሚለውን ጥያቄ አፍኖ ጉዳዩን ለማኀበረ ምእመናን የመጨረሻ ውሳኔ ሳያቀርብ በኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አወቃቀር ከፍተኛ ማዕረግ ላይ ያሉትን ሊቀ ጳጳስ ለማባረር ሙከራ አድርጓል። በተለይም ለእንዲህ ዓይነቱ ከፍተኛ ጉዳዮች ማኀበረ ምእመናን የመጨረሻ ወሳኝ አካል እንደሆነ በምእራፍ 3 አንቀድ 4 ቁጥር 5 በግልጽ አስቀምጦት እያለ አስሩ የቦርድ አባላት ህገ ደንባችንን ጥሰው ለምእመናን እኛ እናውቀለታለን የሚል አምባገነናዊ እርምጃ ወስደዋል።
መ-የእለት ከዕለት አስተዳደራዊ ስራ የሚመፈጽመበት እንዲሁም ዋናውን ህገ ደንብ የሚተርጎመው የውስጠ ደንብ ቦርዱ ከሀገረ ስብከቱ ጋር ያለውን ግንኙነት በገጽ 19 ላይ በግልጽ አቅርቦታል። ቦርዱ ከሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ጋር ያለመግባባት ቢፈጠር የቅዱስ ሲኖዶስ እና የማኃበረ ምእምናን ውሳኔ የመጨረሻ እንደሚሆን ይናገራል። ስለሆነም አስሩ የቦርድ አባላት በማን አለብኝነት መተዳደሪያ ደንባችንን፣ የውስጥ ደንባችንን እና የማኃበረ ምእመናን መብት በሶስት መንገድ የረገጡ እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል።
2- አስሩ የቦርድ አባላት መተዳደሪያ ደንባችን አውጆ የተቀበለውን ህጋዊ ሲኖዶስ አይቀበሉም።  መረጃዎች እነሆ
ሀ-ታላቁ መጽሐፍ የሚቀበለኝ የላከኝ ይቀበላል እንዳለው ህጋዊው ቅዱስ ፓትርያርክ በዚህ መንጋ ላይ የሾሙትን ሊቀ ጳጳስ ያለ  እርሳቸው እና እርሳቸው የሚመሩት ቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የማባረር ሙከራ ።
ለ-ህጋዊ ቅዱስ ሲኖዶስ በብፁእ አቡነ ያዕቆብ የተወሰደውን ህገ ወጥ እርምጃ አውግዞ ቦርዱ ከስህተቱ ታርሞ አቡነ ያዕቆብ አገልግሎታቸውን እንዲቀጥሎ ያሳለፈውን መመሪያ አልተቀበለውም። በተጨማሪም ያለ ሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ የሚካሄዱ ስርዓቶች ቀኖና ቤተክርስቲያንን የጣሱ እንደሆኑና ተቀባይነት እንደማይኖራቸው ቢያውጅም አስሩ ቦርድ እና ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ትእዛዝ አልተቀበሉም።በተጨማሪም ቅዱስ ሲኖዶሱ በተለያየ ጊዜ ያወጣውን መመሪያ እንዳይተገበር የበኩሉን አስተዋጽኦ አድርጓል። ቅዱስ ሲኖዶስ መቀበል ማለት መመሪያ መቀበል ማለት እንደሆነ ለማንም ግልጽ ነው እነ አቶ አየለ፣አቶ አባተ፣አቶ ሽፈራው፣አቶ እሽቱ፣ወ/ሮ አልማዝ እና ካህናቱ በከንፈራቸው ወይስ በልባቸው ህጋዊውን ሲኖዶስ የሚቀበሉት?
ሐ-ቦርዱ በራሱ አምሳል ጠፍጥፎ የሽማግሌ ቡድን ፈጥሮ የህጋዊ ሲኖዶስ ስልጣን ተጋፍቶ በኦርቶዶክሳዊት ቤ/ክ ስርዓት ትውፊት ሆኖ በማያቅ መልኩ ምእመናን ተሰባስበው ለሊቀ ጳጳስ የሱባኤ ቀን ወስነው እንዲሰጡ አድርጓል።


3-ከመቋሚያ አማዛዡ ቦርድ ጀርባ ማን እንዳለ ለማወቅ ወቅቱን የዋጀ  አካሄዳቸውን አስቀድመን እንየው።
ሀ-ወቅቱ  በሀገር ቤት በጎጃም እና በጎንደር እንዲሁም በኦሮም ማኃረሰብ የሚገኙ ወጣቶች ከምንጊዜው በላይ ወያኔ ሲፋለሙ በስደት የሚገኘው ወገናቸው ደግሞ ያለውን የገንዘብ፣የቁሳቁስ ሃይል አሰባስቦ በመርዳት እና አንድ ሆኖ በመጸለይ ነው።ይህን ሃይል ለማዳከም መከፋፈል የሚፈልገው ማነው? እጀ ረዥሙ የወያኔ ቡድን እና ግበረ በሎቹ።
ለ-ገዢው መንግስት የሚቃወሙትን አሸባሪ የሚል የስም ታርጋ መለጠፍ የባህርዩ መገለጫ ነው። የኛዎቹ ጉዶዎች ለማባረር የፈለጉት ሊቀ ጳጳስ ተሃድሶ እንደዚሁም ቀኖና ቤተክርስቲያን እና ህገ ደንብ ይከበር የሚሉትን ምእመናን የተሃድሶ አቀንቃኝ የሚል የስም ታርጋ መለጠፍ የማን ባህርይ ነው? የወያኔ።
ሐ-  የጻፍከውን ህገ መንግስት አክብር ሲባል ህገ መንግስቱን በሃይል ሊንዱ የተነሱ የነውጥ እና የጥፋት ሃይሎች እያለ ወያኔ እመራዋለሁ የሚለውን ህዝብ ያሳድዳል። የኛዎቹም ቦርዶች አረቀቅነው የምትሉት የቤተክርስቲያኗን ህገ ደንብ አክብሩ ሲባሉ በጎጥ የተደራጁ አፍራሽ ሃይሎች ይሉናል። የማን ባህርይ እንበለው? ግልገል ወያኔዎች?
መ-ጎጠኛው የወያኔ ቡድን የሚቃወሙትን  ኦሮሞዎች በሙሉ ጠባቦች  እንዲሁም አማሮችን ትምክህተኞች በማለት በአንድ ቅርጫት ያስቀምጣል። የኛዎቹ ደግሞ ህገ ደንብ እና ቀኖና  ተጣሰ የምንለውን በሙሉ  ጎንደሬዎች በሚል በአንድ ቅርጫት ውስጥ ማስቀመጥ የጎጥ ካርድ መጫወት የማን ባህርይ ነው? ከመምህሩ ደቀ መዝሙሩ እንዲሉ ወያኔ በአንድ ክልል አስቀምጦ የሚያሰቃየውን የአማራን ማህበረሰብ የኛዎቹ ደግሞ በክፍለ ሃገር በመፋፈል በልጠው ተገኝተዋል።
በትክክልም  ለዲያስፓራ በጀት መድቦ በውጭ ሃገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን መከፋፈል ስራዬ ብሎ የያዘው የወያኔ እጅ ከጀርባው እንዳለ የሚያሳዩ አምክንዮዎች ፍንትው ብለው ታይተዋል። አንዳንድ አገራቸው እና ሃይማኖታቸውን የሚወዱ ምእመናን የወሮበላው የወያኔ ተንኮል ባለመረዳት  አጀንዳ አስፈጻሚ እንዳይሆኑ ሊጠነቀቁ ይገባል።
 የጻድቃን መመኪያ የሰማእታት አክሊላቸው የሆነቸውን እመቤታችንን ከሳሽ  ሊቀ ጳጳስ እና ስምንት የቦርድ አባላት ተከሳሽ ብሎ ሽምግልናን ንቆ እንዴት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ  ቤተክርስቲያንን በምእራባውያን ፍርድ ቤት ትቀርባለች። የሚያሳፍረው  በእመቤታችን አማላጅነት እና በታቦት አግልጎሉት የማያምነው ዳኛ ፍርድ እንዲሰጠን  አስሩ የቦርድ አባላት እና አስተዳዳሪው አባ ኃ/ጊዮርጊስ መርጠዋል።  ለቤተክርስቲያናችንን የህንጻ እዳ ለመቀነስ ብለን እንዲሁም ለአመቤታችንን ፍቅር መግለጫ  የሰጠነውን መባ በጠበቃ ወጪ በማባከን ላይም ይገኛሉ።
ወያኔን እፋለማለሁ ያሉ ሁሉ ጸረ ወያኔ እንዳልሆነ የቅንጅቱ አቶ አየለ ጫሚሶን እናስታውሳለን። ወያኔ እየከፈለ ስደቡኝ የሚል የወሮበላ ቡድን እንደሆነ ስለምናውቅ ጨፍኑ  እና ላሞኞቻችሁ በሚለው ብሂል  ባለፈው እሁድ በተከበረው ቤተመቅደስ በታቦተ ህጉ ፊት በአስሩ ቦርድ አፈቀላጤ አማካይነት የተለፈፈው ዲስኩር ያስተዛዝባል።
ይልቁንም ወደ ልባችሁ ተመልሳችሁ  በከንፈር ሳይሆን ከልብ እና በተግባር የቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ተግባራዊ አድርጉ፣ ህገ ደንቡን እና ቀኖና ቤተክርስቲያንን  አክብሩ፣የ305 ምእመናን ድምጽ አክብሩ፣ ከህገ ወጥ መንገዳችሁ ተመለሱ፣ ቤተክርስቲያንን አክብራችሁ አስከብሩ። አሁንም አልመሸም የመዳን ቀን ዛሬ ነውና።
ተክለጊዮርጊስ ዘ አትላንታ

No comments:

Post a Comment

wanted officials