Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Wednesday, November 30, 2016

የአማራ ተጋድሎ ከዚህ ወዴት? ክፍል ሦስት





​(ባለፉት ጊዜያት ክፍል አንድና ሁለት ለአንባቢያን እንዲመች ሆኖ ቀርቧል። ሦስተኛውና የመጨረሻው ክፍል እንሆ፤ ምስጋና በጎንደርና በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ላገዙኝ የአማራ ምሁራን)

ሠ. ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጋር ያለንን ግንኙነት እናሻሽል፤

የሕዝባችን ስም ካለፉት ሥርዓቶች ጋር ተያይዞ የሚነሳው፣ ወይም የአማራ ሕዝብ ባለፉት አገዛዞች እንደተጠቀመ ተደርጎ የሚቀርበው መሠረተ ቢስ ክስ በወያኔና መሰሎቹ ብቻ የሚሰነዘር አይደለም። የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም ቢሆን ለአማራ ሕዝብ ያለው አመለካከት በእጅጉ የተበላሸ ነው። በተለይ በአፍሪካ ቀንድ ላይ ስትራቴጂክ ጥቅማቸውን ለማስከበር በሚራኮቱት ምዕራባውያን ኃያላን አገሮች አካባቢ የአማራ ሕዝብ በአክራሪ ኢትዮጵያዊ ብሔርተኝነት የተፈረጀ ስለሆነ እንዲዳከም ይፈለጋል። በዚህና በሌሎች ምክንያቶች ባለፉት 40 ዓመታት በሕዝባችን ላይ መጠነ ሰፊ ውርጅብኝ ሲደርስ፣ በተለይ ደግሞ ባለፉት ሁለት ዐሥርት ዓመታት በወያኔ ዘረኛ አገዛዝ ሕዝባችን በማንነቱ ምክንያት ከያለበት ሲፈናቀልና ሲሳደድ፣ በሺሕዎች የሚቆጠሩ የአማራ ልጆች ታፍነው እየተወሰዱ በወያኔ ማሳቀያ ቤቶች (አብዛኛዎቹ የአዲስ አበባ ቪላ ቤቶች ናቸው) ውስጥ እየተቆለፈባቸው ሰው ይችለዋል የማይባል መከራ ሲቀበሉ፣

ሰውነታቸው ሲተለተልና ከፍተኛ የሆነ የሥነ ልቦና ጠባሳ ሲደርስባቸው፣ ሲገደሉና ደብዛቸው ሲጠፋ የሚገደው አገርም ሆነ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተቋም አልተገኘም።

በአንድ በኩል ይህ ሁሉ የሚሆነው በእኛ በራሳችንም ድክመት ነው ለማለት ይቻላል። የሕዝባችን መከራ አንገብግቦን አማሮች እንደአማራ ተደራጅተን ባለመንቀሳቀሳችን፣ ብዙ ጥፋት ፈጽመናል። በዘመነ ወያኔ እንደአማራ ሕዝብ የተበደለ፣ እንደአማራ ሕዝብ በጠላትነት የተፈረጀና ስትራቴጂ ተነድፎ እንዲዳከም (በእነሱ አነጋገር አከርካሪቱ እንዲሰበር) የተሠራበት ሕዝብ የለም። ሆኖም ባለመደራጀታችን ምክንያት ይህን በሕዝባችን ላይ ሲፈጸም የቆየውን ጥቃት ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ማስገንዘብ አልቻልንም። እንደሕዝብ ተደራጅተንና ሁላችንም የሕዝባችን ዲፕሎማቶች ሆነን ተንቀሳቅሰን ቢሆን ኖሮ፣ በማያሰልስ ትግልና ውትወታ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የሕዝባችንን በደል እንዲገነዘብ ከማድረግም አልፈን፣ ከኃያላኑ አገሮች ድጋፍ እንኳን ባናገኝ ጠላታችንን ከመደገፍ እንዲቆጠቡ ማድረግ በቻልን ነበር።

የሚያሳዝነው የወልቃይት አማሮች ከ30 ዓመት በላይ ሲገደሉና ሲጮሁ የኖሩ ቢሆንም የወልቃይት ስም በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች እንዲነሳ በርካታ ወገኖቻችንን መገበር ነበረብን። አማሮች በሶማሌ ክልል የተለያዩ ቦታዎች፣ በኦሮሚያ ክልል በአርባ ጉጉ፣ በአርሲ፣ በባሌ፣ በምዕራብ ወለጋ ወዘተ.፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ በደቡብ ክልል በጉራ ፈርዳ፣ በኮንሶ ወዘተ.፣ በአፋር ክልልና በሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከያለበት እየታደኑ ሲገደሉና ሲሳደዱ የደረሰላቸው ኃይል የለም። በአማሮች ላይ ሲደርስ የቆየውንና አሁንም የቀጠለውን መከራ የሚዘግብ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃንም ሆነ የሰብአዊ መብት ተንከባካቢ ተቋም አልተገኘም። ይህም አማሮች እንደሕዝብ ሳንደራጅ ተበትነንና ተዳክመን በመኖራችን ምክንያት የመጣ ችግር ነው። መበተናችን በከፍተኛ አዳክሞናል፤ ለጠላቶቻችን አጋልጦናል። ስለሆነም ካለፉት ስህተቶቻችን ተምረን የዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡን ድጋፍ ለማግኘት ከፍተኛ ትግል ማድረግ ይኖርብናል።

ያለንበት የአፍሪካ ቀንድ በዓለም ላይ እጅግ አስቸጋሪ ከሚባሉት ቀጠናዎች ውስጥ አንዱ ነው። በዚህ አስቸጋሪ ቀጠና ውስጥ ኃያላን አገሮች ብሔራዊ ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ሽኩቻ ሲያደርጉ እንደቆዩና አሁንም በዚኸው ተግባራቸው እንደቀጠሉ ይታወቃል። በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ አሜሪካና አጋሮቹ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት በሚል ምክንያት በዚህ ቀጣና ላይ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እንደሚያደርጉ በግልጽ የሚታወቅ ጉዳይ ነው። የወያኔ መንግሥት የእነዚህ ኃያላን አገሮች የጸረ ሽብር ትግል ጉዳይ ፈጻሚ በመሆኑ ከፍተኛ ድጋፍ ሲደረግለት እንደቆየ፣ እነዚህ ኃያላን አገሮችም ቆመንለታል ከሚሉት የዴሞክራሲና የሰብአዊ መብት ጥበቃ መርሆ ይልቅ ብሔራዊ ጥቅማቸው ስለሚበልጥባቸውና ይህንን ብሔራዊ ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ ደግሞ ከወያኔ የተሻለ አገልጋይ እንገኛለን ብለው ስለማያምኑ፣ ለዚህ ጸረ ሕዝብ ቡደን መጠነ ሰፊ ድጋፍ ሲያደርጉለት ቆይተዋል። ይህ ቡድን የሚፈጽመውን መጠነ ሰፊ የሰብአዊ መብት ጥሰት አይተው እንዳላዩ ሲያልፉ እንደቆዩም ተደጋግሞ የታየ እውነታ ነው።

ነጻነታችንን ማረጋገጥ የምንችለው በራሳችን ትግልና መስዋዕትነት መሆኑ የማያጠራጥር ቢሆንም፣ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰቡን ድጋፍ እስካላገኘን ድረስ፣ ወይም የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለወያኔ የሚያደርገውን ድጋፍ እንዲገታ እስካላደረግን ድረስ የምንከፍለው መስዋዕትነት ከፍተኛ እንደሚሆን ግልጽ ነው። ስለሆነም የሕዝባችን ጥያቄ ፍጹም ፍትሐዊ ጥያቄ መሆኑን፣ የሕዝባችን ትግል ለነጻነት፣ ለእኩልነትና ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚደረግ ትግል መሆኑን ወዘተ. አበክረን ማስገንዘብና የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ከሕዝባችን ጎን እንዲቆም ለማድረግ ያለመታከት መታገል ይኖርብናል።

ይህን ትግል በድርጅትም በግልም ደረጃ መፈጸም ይቻላል። በአማራ ሕዝብ ስም የሚንቀሳቀሱ የሲቪክና የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ የዲፕሎማሲ ሥራና ተዛማጅ ጉዳዮችን የሚሠሩ ክፍሎችን አቋቁመው የኃያላን አገሮችን የፓርላማ አባላትን፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣትን፣ ታዋቂ ሰዎችን፣ ምሁራንና ተመራማሪዎችን፣ ጋዜጠኞችንና የሰብአዊ መብት ተንከባካቢ ድርጅቶችን ወዘተ. ሳይታክቱ ማስረዳትና ሳያሰልሱ መወትወት ይገባቸዋል። ሥራው በቋሚነትና ያለመታከት የሚሠራ እንጂ ብልጭ ድርግም የሚል የአንድ ሰሞን ሆይ ሆይታ መሆን የለበትም። በግለሰብ ደረጃም ቢሆን ይህንን ሚና መወጣት ይቻላል። ከዚህ ወሮበላ ቡድን ጋር እየታገለ የሚሞተው ወገናችን በደል አንገብግቦን፣ ሁላችንም የሕዝባችን ዲፕሎማቶች ሆነን መንቀሳቀስ ይኖርብናል፤ እንችላለንም። አንድ የውጭ መገናኛ ብዙሃን የሚሠራው ዘገባ፣ አንድ የታወቀ ምሁር የሚሠራው ጥናታዊ ጽሑፍ፣ አንድ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተንከባካቢ ድርጅት የሚያዘጋጀው ሪፖርት ወዘተ. በጣም ትልቅ ዋጋ አለው። ትግሉ ዘርፈ ብዙ ነውና በዚህም ረገድ ከፍተኛ ሥራ እንድንሠራ ያስፈልጋል።

ረ. በመናበብ እንታገል፤

በጣም በርካታ የአማራ ልጆች ሕዝባችን እንደሕዝብ ተደራጅቶ መብቱን ከማስከበርና ክብሩን ከማስጠበቅ ውጪ ምርጫ የለውም ብለው፣ ሌት ተቀን በአማራ ጉዳይ ላይ እየሠሩና እየታገሉ ነው። የአዲሱ ታሪክ ሠሪ የአማራ ትውልድ አባላት ሕዝባችን በአማራነቱ እንዲደራጅ፣ በአማራ ሕዝብ ስም የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካና የሲቪክ ድርጅቶች በጋራ፣ በትብብርና በመናበብ እንዲሠሩ ሳያሰልሱ ይጽፋል፤ ይታገላሉ። በአማራ ሕዝብ ላይ እየደረሰ ስለሚገኘው ፍጅት መረጃዎችን እያሰባሰቡ ለሕዝባቸው ያደርሳሉ፤ የነብሰ ገዳዩን ፋሽስታዊ ቡድን ጽረ አማራ ድርጊት ከሥር ከሥር እየተከታተሉ ያጋልጣሉ፤ ሕዝባችን ሊወስድ ስለሚገባው እርምጃ አቅጣጫ ይጠቁማሉ፤ ከጠላት ጋር ይተናነቃሉ፤ ለአማራ ሕዝብ መስዋዕት እየሆኑ ሕዝባቸውን ነጻ ለማውጣት ሌት ተቀን ከጠላት ጋር ይዋደቃሉ። በእርግጥም ይህ ታሪክ ሠሪ ትውልድ ታሪክ መሥራት ጀምሯል!! በልጆቻችን መካከል ይበልጥ የመቀናጀት፣ ይበልጥ የመናበብና አብሮ የመሥራት ልምድ እንደሚዳብር እና ሕዝባችን የጀመረውን እልህ አስጨራሽ ትግል በድል እንደሚወጣ አንዳችም ጥርጣሬ የለንም። የሕዝባችን ህልውና ለመጠበቅ እንደአማራ ከመደራጀት ውጪ ምንም ዓይነት ምርጫ የለንም። እንደአማራ እናስብ፣ እንደአማራ እንደራጅ፣ ለአማራነት እንሰዋ!!!!

እንደሚታወቀው የትግሉ መሪም አንቀሳቃሽም አገር ቤት ያለው ሕዝብ ነው። የሚሞተውም የሚታሰረውም የቶርቸር ሰለባ የሚሆነውም እሱ ነው። በግልጽ እንደሚታየው ሕዝባችን ከወያኔ ዘረኛ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት ከነብሰ ገዳዩ አጋዚ ጋር እየተዋደቀና ከፍተኛ መስዋዕትነት እየከፈለ ነው። ይህ ሕዝብ ሊደገፍና ‹አይዞህ› ሊባል ይገባዋል። የሕዝባችን የስቃይና የመከራ ጊዜ እንዲያጥርና መስዋዕትነቱ እንዲቀንስ ተጋድሎውን ሳያሰልሱ መደገፍ ያስፈልጋል። በዚህ ረገድ የሕዝባችን ትግል በመደገፍና ልዩ ልዩ አስተዋጽዖ በማድረግ ከፍተኛ እንቅስቃሴ የሚያደርጉ ድርጅቶች በውጪ አገሮች በመንቀሳቀስ ላይ ናቸው። እነዚህ ድርጅቶችና የድርጅቶቹ አባላት የሕዝቡን ተጋድሎ ሌት ተቀን እየደገፉና ትልቅ አስተዋጽዖ እያደረጉ ይገኛሉ።

እንደቤተ አማራ፣ ሞረሽ፣ ዳግማዊ መዐሕድ ወዘተ. ያሉ አማራ ድርጅቶች ይበልጥ እንዲጠናከሩና እንዲጎለብቱ መደገፍ ይገባናል። እነዚህ ድርጅቶች ራሳቸውን በገንዘብና በሰው ኃይል አቅም እንዲያጎለብቱ፣ የጥናትና ምርምር፣ የመረጃና የሕዝብ ግንኙነት፣ የፋይናንስ ወዘተ. ክፍሎች እንዲኖሯቸውና መሠረት ያለው ሥራ መሥራት እንዲችሉ ጠንካራ ድጋፍ ሊደረግላቸው ይገባል። ከዚህም በላይ የወያኔን ጸረ አማራ አገዛዝ ማስወገድ የሚቻለው በትጥቅ ትግል ጭምር ነውና በአማራ ስም የሚንቀሳቀሱ ታጋይ ድርጅቶችን መደገፍም ያስፈልጋል (ብዙ ወገኖች በአማራ ሕዝብ ስም የሚንቀሳቀሱት ድርጅቶች እንዲዋሐዱ ተደጋጋሚ ጥሪ እንደሚያቀርቡ ይታወቃል። እነዚህ ወገኖች የአማራ ድርጅቶች እንዲዋሐዱ የሚወተውቱት፣ ድርጅቶች በፋይናንስ፣ በሰው ኃይልና በድርጅታዊ አቅማቸው እንዲጎለብቱ ከመፈለግ እንደሆነ ግልጽ ነው። ሆኖም የአማራ ድርጅቶች እርስ በርሳቸው እየተናበቡና እየተደጋገፉ እስከሠሩ ድረስ፣ ይልቁንም አንዱ ሌላውን ለማጥፋት እስካልሠራ ድረስ የግድ መዋሐድ አለባቸው ማለት አይደለም።

የአማራ ሕዝብ በቁጥር ብዙ ነው፤ የገጠሙን ፈተናዎችም በርካታ ናቸው። ስለሆነም እነዚህን ፈተናዎች ለመወጣት ሁሉም ድርጅቶች ለትልቁ ዓላማ (አማራን ነጻ ለማውጣትና የሥልጣኑ ባለቤት ለማድረግ) እስከሠሩ ድረስ ብዙ ድርጅቶች መኖራቸውና የተለያዩ የትግል ስትራቴጂ መከተላቸው የሚጠበቅና ተፈጥሯዊ ነው። ቁም ነገሩ ሁሉም ለትልቁ ዓላማ መሥራታቸው ነው። አንድ ድርጅትና አንድ ስትራቴጂ የሚለው አካሔድ በብዙ መልኩ ተጨባጭ (realistic) ያልሆነና ከዘመኑ ጋር የማይሔድ ነው። በውስጣችን ያለውን የአመለካከት ብዝሃነት አክብረን ሁላችንም ለትልቁ ዓላማ ከሠራን ውጤታማ የማንሆንበት ምንም ምክንያት የለም። በድርጅቶች መካከል የሚኖር መተባበር አስፈላጊ የሆነውን ያህል ጤናማ ውድድርም መለመድና መደገፍ አለበት። መጥፋት ያለበት ‹መጠፋፋት› ነው። እሱ ነቀርሳ ነው። ከእስራኤል ድርጅቶች እንማር!!!)። ሁሉም አማራ እንደቀደመ ባህሉ ራሱን አስታጥቆ በተፈለገበት ጊዜ እየተጠራ ራሱን እንዲከላከል (በcitizen army መልክ) ለማድረግም ልዩ ልዩ ዘዴዎችን ማዘጋጀት ያስፈልገናል። ሕዝባችን በሕዝባዊ ሠራዊትነት ከታጠቀና ከተደራጀ ከጎያው ውስጥ ያሉትን ምንደኞችም ሆነ ቀንደኛ ጠላቱን ማንኮታኮት ይችላል። ስለሆነም በዚህ ሕዝባችንን በማደራጀትና በማስታጠቅ ረገድም ብዙ ሥራ ይጠብቀናል (በዚህ ረገድ ከሕዝባችን ነባር ባህል በተጨማሪ የእስራኤልንና የታይዋንን ተሞክሮ አካቶ ብዙ መሥራት ይቻላል።)።

እነዚህን ሁሉ ሥራዎች ለመሥራት በአማራ ድርጅቶች ዘንድ መናበብ እንዲኖር ያስፈልጋል። እጅግ በጣም ያስፈልጋል። ሁሉም ርካሽ ለሆነው የግል ዝና ወይም የድርጅት ጥቅም ሳይሆን ለትልቁ ሕዝባዊ ዓላማ፣ ሕዝባችን ከወያኔ ጸረ ሕዝብ አገዛዝ ነጻ ለማውጣትና አንገቱን ቀና አድርጎ እንዲሔድ ለማስቻል ተቀናጅቶና ተናቦ መሥራት ይኖርበታል። ለግል ዝና ወይም ጠባብ ለሆነ ድርጅታዊ ጥቅም መሯሯጥ በሞቱት ወንድሞቻችንና እህቶቻችን አጥንት ላይ መሳለቅ ነው!!! ርካሽነት ነው!!! በማደግ ላይ ባለው የአማራ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ብሔርተኝነት ላይ ውኃ መቸለስና ሕዝብን ለባርነት ማመቻቸት ነውና ጨርሶ አዝማሚያውም መታየት የለበትም!!!

የየድርጅቶቻችን ህልውና ይዘን፣ ነገር ግን በጋራና በተቀናጀ ሁኔታ ለትልቁ ዓላማ መሥራት ይኖርብናል። እንወያይ፤ እንመካከር፤ በጋራ ለጋራ ዓላማ እንሥራ፤ ተቀናጅተንና ተናበን እንታገል። ማግለል፣ መፈራረጅ፣ መቧደን፣ መጠፋፋት፣ ቂመኝነት፣ ሐሜትና አሉባልታ ብዙ የአማራ ልጆችን አስፈጅተው አይወድቁ አወዳደቅ ከወደቁት ከ1960ዎቹ እና ከዚያም በኋላ ከተመሠረቱት ድርጅቶች የመጣ ርካሽ አስተሳሰብ ነውና የዚህ ርካሽ አስተሳሰብ ሰለባ እንዳንሆን ሁልጊዜም እንጠንቀቅ!!!

ወያኔ የብሔረሰብ ደርጅት መሆኑ ብቻ ሳይሆን ላለፉት ሁለት ዐሥርት ዓመታት መላ ኢትዮጵያን ተቆጣጥሮ ይህ ነው የማይባል ሀብት ያጋበሰ፣ ግዙፍ የቢዝነስ ኢምፓየር የገነባ፣ የኢትዮጵያን የመከላካያና የጸጥታ ተቋማት ሙሉ በሙሉ በእጁ ያደረገ፣ ከወያኔ ጋር ተጠጋግቶ በአንድ ጀንበር ሀብት ያፈራና ወያኔን ለመጠበቅ የማያመነታ ከበርቴ ቡድን ከጎኑ ያሰለፈ ግፈኛ ቡድን በመሆኑ እንዲህ በቀላሉ ይንኮታኮታል ብለንም አናምንም። ይህ ጸረ ሕዝብ ቡድን የሀብቱና የምቾቱ ምንጭ የሆነውን ሥልጣኑን ለማስጠበቅ ሲል የማይፈነቅለው ድንጋይ እንደሌለ የተገደሉት፣ የተሰደዱትና በገፍ የታሰሩት ወገኖቻችን፣ እንዲሁም በቅርቡ ያወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በቂ ማስረጃዎች ናቸው። ወደፊትም ቢሆን ሥልጣኑን ለማስጠበቅ ወገኖቻችን ይገድላል፣ ያስራል፣ ያሳድዳል።

ሆኖም እንደ ሕዝብ ከተደራጀን ወያኔን ከሕዝባችን ጫንቃ ላይ አሽቀንጥረን ጥለን ነጻነታችንን ማወጅ እንደምንችል ደግሞ አንጠራጠርም። በእኛ በኩል የአማራ ሕዝብ የተደቀነበትን የዘር ፍጅት አደጋ ለመቋቋም፣ ነጻነቱን ለማረጋገጥና ከዚያም በኋላ ዘላቂ ጥቅሙን ለማስጠበቅ እንደሕዝብ መደራጀትና መታገል አለበት የሚል የማያወላውል አቋም አለን። ይህ በሕዝብ ደረጃ ተደራጅቶ የመታገልና ዘላቂ ጥቅምን የማስከበር ጥረት ተጀምሮ የሚቆም የአንድ ዘመን እንቅስቃሴና የአንድ ሰሞን የወረት እንቅስቃሴ አይደለም። ‹የአማራ ተጋድሎ እስከ ወያኔ ውድቀት ብቻ የሚዘልቅ ነው፣ ወይም የሕዝባቸን ተጋድሎ ወያኔን በመጣል የሚጠናቀቅ ነው› የሚል ብዥታም ጨርሶ የለንም። ይልቁንም በእኛ እምነት በአማራነት መደራጀታችንም ሆነ የምናደርገው ተጋድሎ ሕዝባችን እስካለ ድረስ የሚቀጥል የማያቋርጥ ሒደት ነው። ወያኔ መውደቁ ለሕዝባችን ትልቅ ድል ቢሆንም፣ የአማራ ሕዝብ ጥያቄ ከወያኔ ባሻገር የሚሔድ መሆኑ ግን በሚገባ ሊሰመርበት ይገባል። በእኛ እምነት ጠንካራ ድርጅቶች የሚያስፈልጉንም ለዚህ ነው።

በሕዝብ ስም የተቋቋሙት ድርጅቶች ሊዳከሙ፣ ከዚያም አልፎ ተፈጥሯዊ ሞት ሊሞቱ ይችላሉ። ሆኖም ሕዝቡ እስካለ ድረስ አንድ ድርጅት ሲዳከም ወይም ሲሞት፣ ሌሎች በርካታ ድርጅቶች እየተወለዱና እየተጠናከሩ ይቀጥላሉ እንጂ ከዚህ በኋላ ሕዝባችን እንደሕዝብ ሳይደራጅ ተበትኖ የግፈኞች የጥቃት ሰለባ የሚሆንበት ምንም ዓይነት ሁኔታ አይኖርም። ደጋግመን እንደምንለው የአማራ ሕዝብ በወያኔ ከታወጀበት የዘር ፍጅት ጦርነት ራሱን መከላከል የሚችለው እንደሕዝብ ሲደራጅ ብቻ ነው። ከወያኔ መንኮታኮት በኋላ ዘላቂ ጥቅሙን ማስከበር የሚችለውም እንደአማራ ሲደራጅ ነው። አዲሱ የአማራ ትውልድ ይህን መሠረታዊ ሐቅ በሚገባ ተገንዝቦ እየታገለና ውድ ዋጋ እየከፈለ ይገኛል።

እንደሕዝብ ከተደራጀን ለአማራ ሕዝብ ነጻነት ሲሉ መስዋዕት የሆኑ ወገኖቻችን መስዋዕትነት እንዲሁ መና ሆኖ የሚቀር አይሆንም። ስለሆነም እንደአማራ ተደራጅተን ወገኖቻችን የተነሱለትን ዓላማ ከግቡ ለማድረስ እየተንቀሳቀስን፣ እዚያው በዚያው እነሱ የሚታወሱበትን መንገድም መቀየስ ይኖርብናል። የተሰውትን ወገኖቻችን ማንነትና እንዴት መስዋዕት እንደሆኑ በዝርዝር ሰንዶ መያዝ፣ በስማቸው ልዩ ልዩ ተቋማትን መመሥት፣ ቤተሰቦቻቸው እንዳይበተን ልዩ ልዩ ድጋፍ ማድረግ ወዘተ. ወዘተ. ይገባናል።
ከዚህም በላይ እስካሁን የመጣንበትን የትግል ሒደት፣ በትግላችን ያገኘናቸውን ስኬቶችና ያመለጡንን ዕድሎች በሚገባ መርምረንና ከአገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ አንጻር ቃኝተን ልዩ ልዩ የትግል ስትራቴጂዎችን መቀየስ ይገባናል። ብዙ ርቀት የመጣን ቢሆንም አሁንም ገና ብዙ ሥራ እንደሚጠብቀን ተገንዝበን አምርረን መታገል ይጠበቅብናል። እነዚህንና ሌሎች ተግባሮችን ለመወጣት ደግሞ ሁላችንም በጊዜ የለኝም መንፈስ መሥራት እና እርስ በርሳችን መናበብና መደጋገፍ ይኖርብናል። ገዳዮቻችን እኛን ለማጥፋት ሌት ተቀን እየሠሩ ነው። እኛም አጥፊዎቻችን ለማጥፋትና ራሳችንን ከጥፋት ለመታደግ ያለ እረፍት ከመሥራት ውጪ ምርጫ የለንም። እነሱ እያሉ ሰላም አይኖረንምና ከእነዚህ ጸረ አማራ የባንዳ ልጆች ራሳችንን ለመገላገል ሁላችንም (በምንችለው መንገድ ሁሉ) ሌት ተቀን እንታገል። በትግላችን ነጻነታችንን እናረጋግጣለን!!!

ሰ. ቀጣይነት ያለውና ሁሉዐቀፍ የሆነ ትግል እንታገል፤

የተጋረጠብን ፈተና በጣም ግዙፍ ሲሆን፣ የገጠመን ወደረኛም በእጅጉ የተደራጀ ነው። ስለሆነም ከላይ እንደተገለጸው ትግላችን ከወረተኛነት የተላቀቀ፣ ቀጣይነት ያለውና ከሚገጥሙን አገራዊ፣ ቀጠናዊና ዓለም አቀፋዊ ፈተናዎች አንጻር እየተቃኘና እየሻሻለ የሚሔድ እንዲሆን ያስፈልጋል። በውሱን ድሎች ረክተን፣ ወይም በአንድ ግጥሚያ (battle) ላይ በሚደርስብን ሽንፈት ተስፋ ቆርጠንና ተሸመድምደን ከዋናው ግባችን የምናፈገፍግ መሆን የለብንም። የአርበኞች አባቶቻችን የተጋድሎ ታሪክ የሚያስተምረን ወረተኝነትንና የአንድ ሰሞን ሆይ ሆይታን ሳይሆን፣ አይቻልም በሚባሉ ፈተናዎች ውስጥ በጽናትና በአይበገሬነት ማለፍን በመሆኑ ሁላችንም (በምንችለው ዘዴ ሁሉ) በጽናት መታገል ይኖርብናል።

በሌላ በኩል ትግላችን በአንድ የትግል ስልት ላይ ብቻ የተንጠለጠለ ሳይሆን ሁሉዐቀፍ እንዲሆን ያስፈልጋል። ትግላችን በመሬት አንቀጥቅጥ ሰላማዊ ሰልፍና በቤት ውስጥ አድማ፣ ሕዝባችን በሚያስገድሉ ወያኔዎችና ምንደኞች ላይ እርምጃ በመውሰድ፣ የወያኔ የአፈና ተቋማት እንዳይሠሩ ቴክኖሎጂ ተጠቅሞ በማሽመድመድ፣ የሕዝባችን በደል በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት እንዲያገኝ የዲፕሎማሲ ትግል በማድረግ ወዘተ. ብቻ የሚወሰን አይደለም። ጠንካራ ሕዝባዊ ሠራዊትም ያስፈልገናል። እነዚህ ሁሉ የትግል መስመሮች እርስ በርሳቸው የሚደጋገፉና የሚመጋገቡ ናቸው። በአንዱ ስልት ብቻ ተንጠልጥለን ሌሎችን ስልቶች ገሸሽ ማድረግ የለብንም። የተራዘመ የትጥቅ ትግል አስበንና በእሱ ላይ ብቻ ተንጠልጥለን ሁሉንም ነገር እርግፍ አድርገን ከተውነው ትልቅ ዋጋ እንከፍላለን። በከተሞቻችን ውስጥ በሚደረግ ሕዝባዊ እምቢተኝነትና ተጋድሎ ላይ ብቻ ከተንጠለጠልንም አሸናፊ መሆን አንችልም። መፍትሔው ቀጣይነት ያለውና ሁሉዐቀፍ የሆነ ትግል መታገል ነው።

#የአማራ_ተጋድሎ ይቀጥላል!!!

No comments:

Post a Comment

wanted officials