Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Monday, July 13, 2015

አርበኞች ግንቦት 7 የከፈተው ወታደራዊ ጥቃት ከወልቃይት ወደ አርማጭሆ በመስፋፋት እንደቀጠለ ነው


አርበኞች ግንቦት 7 የከፈተው ወታደራዊ ጥቃት ከወልቃይት ወደ አርማጭሆ በመስፋፋት እንደቀጠለ ነው



~የአርበኞች ግንቦት 7 ህዝብ ግንኙነት~

አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ በህወሓት መራሹ መከላከያ ሰራዊት ላይ የከፈተው ወታደራዊ ጥቃት ከወልቃይት ወደ አርማጭሆ በመስፋፋት በእጅጉ ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው፡፡

ዘረኛውና ፋሽስቱን የህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ ቡድን በጠብመንጃ አምበርክኮ ህዝቡን ብቸኛው የስልጣን ባለቤት የማድረጉ የትጥቅ ትግል ከኤርትራ በረሃዎችና ጠረፎች አልፎ በኢትዮጵያ መሬት ላይ በአስተማማኝ ሁኔታ እግሩን በመትከሉ ህወሓት ለእርድ ያሰናዳው ሰራዊት ከአርበኞች ግንቦት 7 አርበኛ ታጋዮች ብቻ ሳይሆን ከወልቃይትና አርማጭሆ ህዝብ በያቅጣጫው እየተከፈተበት የሚገኘውን ፋታ የሌለውና ጠንከር ያለ የተኩስ ናዳ ፈፅሞ መቋቋም አልቻለም፡፡

ከሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች በአውቶብስ እያጋዘ ሰሜን ኢትዮጵያ ላይ ያከማቸው መከላከያ ሠራዊቱ የአርበኞች ግንቦት 7 ጀግና የነፃነት ፋኖዎች ከህዝብ ጋር ተቀናጅተው ባልጠበቀው ጊዜና ሁኔታ የሚከፍቱበትን የጎሬላ ውጊያ ጥቃት ገና ካሁኑ መመከት ተስኖት ከጦር ሜዳ መሸሽ እና መክዳት በመጀመሩ ህወሓት እንደ ድጋፍ ሰጪም እንደተወርዋሪም የሚጠቀምባቸውን የፌደራል ፖሊስ፣ ልዩ ኃይል፣ ፀረ-ሽምቅ እና ሚሊሻ ኃይሎችን በተጓዳኝ በገፍ አስፏል፡፡

መከላከያን ጨምሮ በእነዚህ ድጋፍ ሰጪ ኃይሎች መካከል አለመረጋጋት እና በራስ አለመተማመን የወለደው የለየለት መተራመስ በመስፈኑ በህዝቡና በአርበኞች ግንቦት 7 የጎሬላ ተዋጊዎች እየደረሰባቸው ሚገኘውን ጥቃት ተቀናጅተው መመከት አልቻሉም፡፡

በመሆኑም ከትናንት በፊት ሀምሌ 3 2007 ዓ.ም ታች አርማጭሆ ጎደቤ ላይ ልዩ ኃይል እና ፀረ-ሽምቅ ጎራ ለይተው በመሰላለፍ እርስበርሳቸው ውግያ ውስጥ ገብተው በጥይት ተጠዛጥዘዋል፡፡ በእነኚህ ተስፋ የቆረጡ ሁለት የታጠቁ ኃይሎች መካከል በተደረገው ለሰዓታት የዘለቀ ውግያ በትንሹ ስድስት አባላት ሲሞቱ በርካቶች ደግሞ ቆስለዋል፡፡

የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ አርበኛ ታጋዮች ህወሓት በገፍ ያሰለፈውን የመከላከያ፣ ፌደራል ፖሊስ፣ ልዩ ኃይል፣ ፀረ-ሽምቅ እና ሚሊሻ ጦር መውጭያ መግቢያና ማረፊያ ነስተው ቁምስቅሉን ከማሳየታቸው ጎን ለጎን የድርጅቱን ህዝባዊ ዓላማ እና ፕሮግራም በበራሪ ወረቀት መልክ ከመተማ እስከ ጎጃም ለሚገኘው ህብረተሰብ በማድረስ ላይ ይገኛሉ፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials