Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Monday, July 27, 2015

ግንቦት7ትና ድርጅቶች "የሽብር ዝንባሌ እንደሌላቸው የእኛ የመረጃና የደህንነት መረጃዎች ያሳዩናል"ፕ/ት ኦባማ

ሐምሌ ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- አሜሪካዊው ፕ/ት ባራክ ኦባማ ይህን የተናገሩት " በአሜሪካና በኤርትራ የሚገኙ የተቃዋሚ ድርጅቶች ኢትዮጵያ ሽብርተኝነትን ለመወጋት የምታደርገውን ጥረት እያደናቀፉ በመሆኑ የእርስዎ መንግስት የኢትዮጵያን መንግስት ለመርዳት ምን ያክል ዝግጁ ነው ተብሎ ከኢቢሲ ጋዜጠኛ " ጥያቄ መቅረቡን ተከትሎ ነው። ጋዜጠኛው የድርጅቱን ስም በግልጽ ከመግለጽ ቢቆጠብም፣ ፕ/ት ኦባማ የሰጡት መልስ ፣ የኢህአዴግ ባለስልጣናት ከዚህ ቀደም ለአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት ምክትል ሃላፊ ዌዲ ሸርማን አርበኞች ግንቦት7ትን በአሸባሪነት እንዲፈረጅ ያቀረቡትን ጥያቄ፣ ለፕ/ት ኦባማም ማቅረባቸውን የሚያመለክት ነው። ፕ/ት ኦባማ በመልሳቸው " ፖሊሲያችን መንግስትን በሃይል ከስልጣን ማውረድን አይደግፍም፣ ይህ ፖሊሲያችን በዲሞክራሲያዊ ሁኔታ የተመረጠውን የኢትዮጵያን መንግስትንም ያካትታል" ካሉ በሁዋላ፣ "በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ከፍተኛ ችግር እየፈጠሩብኝ ነው በማለት የሚፈርጃቸው ድርጅቶች እንዳሉ እናውቃለን፣ ይሁን እንጅ በመንግስት ላይ ተቃውሞ ቢያሰሙም የሽብር ዝንባሌ እንደሌላቸው የእኛ የመረጃና የደህንነት መረጃዎች ያሳዩናል" በማለት በኢህአዴግ መንግስት በኩል የቀረበውን ጥያቄ ሳይቀበሉት መቅረታቸውን ተናግረዋል። "ይህንን በመገምገም በኩል ግልጽ የሆነ መስፈረት አለን ያሉት ኦባማ፣ ለወደፊቱ እነዚህ ድርጅቶች የሽብር ጥቃት ይፈጽማሉ አይፈጽሙም የሚለውን ለወደፊቱ የምናየው ይሆናል ብለዋል። " አንድ ድርጅት የፖለቲካ ተቃውሞውን ቢገልጽ ፣ ከአስተሳሰቡ ጋር ባንስማማም እንኳ ከለላ እንሰጠዋለን፣ ይሄ በአሜሪካ በሌላም ቦታ የሚሰራበት እውነታ ነው፤ ይህን ማድረግ ለዲሞክራሲ እድገት አስፈላጊ ነገር ነው " አሉት ኦባማ ፣ ድርጅቶቹ ወደ ሃይል ሲያዘነብሉና በህገመንግስት የተቋቋመን መንግስት ለመገልበጥ ሲሞክሩ፣ ድርጊቱ ያሳስበናል። " በማለት መልሰዋል። የውጭ አገር ጋዜጠኞች ፣ በእስር ላይ ስለሚገኙ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች እንዲሁም ስለኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት አያያዝ ጉዳይ ለፕ/ት ኦባማና ለአቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ጥያቄዎችን አቅርበዋል። ፕ/ት ኦባማ በኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ጥበቃ እና በዲሞክራሲ ዙሪያ ከአቶ ሃይለማርያም ጋር ሰፊ ውይይት ማድረጋቸውን፣ አሜሪካ በቅርብ ሁና እገዛ ለመስጠት መዘጋጀቷን ገልጸዋል። የኢህአዴግ መንግስት ከፕ/ቱ ጉብኝት በዋናነት የሚጠብቀው ለስልጣኑ ስጋት የሚፈጥሩ ድርጅቶች በሽብረተኝነት እንዲፈረጁለት ቢሆንም፣ ይህንን ሳያገኝ ቀርቷል። ይሁን እንጅ ባራክ ኦባማ የኢህአዴግን መንግስት በዲሞክራሲያዊ ምርጫ የተመረጠ ነው ማለታቸው በርካታ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችን ሳያስቆጣ አይቀርም። ኦባማ በአንድ በኩል በኢትዮጵያ እየጠበበ ስለመጣው የፖለቲካ ምህዳር ሲናገሩ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ምርጫውን ዲሞክራሲያዊ የሚል ካባ ማላበሳቸው፣ የአሜሪካ የውጭ ፖሊስን ተቃርኖ የሚያሳይ ነው።
Barack Obama, right is greeted by Ethiopian Prime Minister Hailemariam Desalegn. 26 July 2015
 በሌላ በኩል ኢ/ር ይልቃል ለፕሬዝደንት ኦባማ በተዘጋጀው የእራት ግብዣ ላይ እንደማይገኙ አስታውቀዋል። የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት መንግስት ሀምሌ 20/2007 ዓ.ም ምሽት 1፡00 ሰዓት ላይ ቤተ መንግስት ውስጥ ለአሜሪካው ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ የሚያደረገውን የእራት ግብዣ ያልተቀበሉት፣ ‹‹ አሸባሪ አድርጎ የሚቆጥረን ኢህአዴግ፣ ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ ሲመጡ በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ለማስመሰልና ዕውቅና ለማግኘት ያደረገው በመሆኑ አልገኝም›› ብለዋል፡፡ ኢ/ር ይልቃል አክለውም ‹‹የኢትዮጵያ ህዝብ ጭቆና እና ስቃይ ውስጥ ባለበት በአሁኑ ወቅት ኢህአዴግ የጠራው የቅንጦት ግብዣ ላይ መገኘት የህዝቡን ሰቆቃ እንደመርሳት እቆጥረዋለሁ›› ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል የአሜሪካው ፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ መግለጫ በሚሰጡበት ወቅት ኢህአዴግ በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው ማለታቸው ቅር እንዳሰኛቸውም ሊቀመንበሩ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ኢህአዴግን በዴሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ነው ማለት የሰላማዊ ታጋዮችን ስቃይ የሚክድና ለአምባገነኖች ይሁንታ የሚሰጥ ነው›› ሲሉ የፕሬዝደንት ኦባማን ንግግር ነቅፈውታል፡፡ ፕሬዝደንት ኦባማ የጠበንጃ ትግልን አለመደገፍን ለመግለፅ የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንትን ጨምሮ ሌሎች የአሜሪካ ተቋማት ኢ-ዴሞክራሲያዊ መሆኑን አረጋግጠውት፣ መቶ ፐርሰንት ምርጫ አሸንፌያለሁ የሚልን ፓርቲ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ እንደተመረጠ መግለፃው እንዳሳዘናቸው ኢ/ር ይልቃል ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment

wanted officials