Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, July 30, 2015

ያንዳርጋቸው ላፕ-ቶፕ ( ሄኖክ የሺጥላ )

ያንዳርጋቸው ላፕ-ቶፕ ( ሄኖክ የሺጥላ )
ቻይናዊው ጠሐፊ ሱን ዙ << የጦርነት ጥበብ >> ( The Art of War ) በተባለው መጽሐፋቸው ፣ በምዕራፍ 4 ፣ ስልታዊ መሰናስኖች ወይም በፈረንጂኛው ( Tactical Dispositions ) በሚለው ዘውግ አርዕስት (Sub title ) ስር እንዲህ ይላሉ ፣ << To secure ourselves against defeat lies in our own hands, but the opportunity of defeating the enemy is provided by the enemy itself >>። ይህንን እንደወረደ ( በግርድፉ ) ወደ አማርኛ ብቀዳው << ራሳችንን ከተሸናፊነት ለመጠበቅ የሚያስችለው ነገር በራሳችን እጅ ላይ ያለ ሲሆን ፣ ጠላታችንን ለማሸነፍ የሚያስችለውን ዕድል ግን ራሱ ጠላታችን የሚያመቻቸው ነው >> ይላሉ ።
ከምናየው ፣ ከደረሰብን እና ከምንረዳው ተነስተን እኛም አንድ ነገር መናገር እንችላለን ። ለቀጣዩ ትግል ራሳችንን ማዘጋጀት እና ወደ ትግሉ ጎራ መቀላቀል በኛ እጅ ያለ ሲሆን ፣ ራሳችንን የምንሰዋለት ትግል ፍሬያማነት ግን ከሞላ ጎደል እየተሳካ ያለው ፣ ወያኔ ( ህውሃት ) እያመቻቸልን ባለው እድል ነው ። የእድል ስም ዝርዝሮቹ በጥቂቱ የሚከተሉት ናቸው
1) የህዝቦች እኩልነትን ፣ እኩል ባለመሆን ሲያከብር 
2) ምርጫ ዝንተ ዓለም ፣ ከስልጣን ዝንተ ዓለም ጋ ፣ ጋብቻ ፈጽመው ፣ እንከን በሌለው ሁናቴ ሕዝቡን በነጻነት ለመጨቆን የወሰኑ ለት 
3) ሕዝብ ጉልበት የለውም የሚል ስርዓት ፣ የሕግና የሕገ መንግስት አርቃቂ እና ተርጏሚ ሲሆን 
4) በማፈን ፣ በማሰር ፣ በመግደል እና በመዋሸት ሀገር ይመራል ብሎ በጽኑ የሚያምን ድርጅት ፣ የእድገት እና የለውጥ ሐዋርያ ስለመሆኑ ሲደሰኩር እና ሲደሰኮርለት 
5) የእቃቃ ዘመኑን በጫካ አሳልፎ ፣ በአባወራ እድሜው እቃቃ የሚጫወት ጎልማሳ እና ሽማግሌ ባለስልጣን ፣ እሱ ከሌለ ሀገር እንደሚፈር እንድናምን ለማድረግ ሲሞክር 
6) ነጻነት እንደ ቅንጦት በሚታይበት ሀገር ፣ ተመሳሳይ የሽብር ዘገባዎችን ፣ ጥናታዊ ፊልሞችን ፣ ክሶችን ፣ እና ውንጀላዎችን እያጠናቀረ ፣ ሕዝቡን የሚያምስ ስርዓት ፣ የፖለቲካ እስረኞች ፣ ጋዜጠኞች ፣ አረጋውያን እና ወዘተ ፣ በማረፊያ ቤት ቆይታቸው በቂ የህክምና አገልግሎት እንዳያገኙ ብቻ ሳይሆን በህክምና ፣ በምግብ ፣ እና በመሳሰሉት ነገሮች እጦት እንዲሰቃዩ በማድረግ የሚታወቅ ስርዓት ፣ ስለ እስረኛዎች እንክብካቤ ሲያወራ እና ሲተርክ
እነዚህ እና ሌሎች እልፍ ምክንያቶች ጠላታችንን ለማሸነፍ ፣ ጠላታችን ራሱ የሚያመቻቸው ነገሮች << the opportunity of defeating the enemy is provided by the enemy itself >> የተባለውን እንደሚወክል ነው ።
በነገራችን ላይ ፣ ታጋይ ቴዎድሮስ አድሃኖም ፣ አንዳርጋቸው ላፕ-ቶፕ እንደተሰጠው ፣ መጽሐፍም ጽፎ እንደጨረሰ ፣ አዳማንም አይቶ << ፑ ! አዳማ ! ያንቺን እድገት ሳላይ አስመራ በርሃ ላይ ባለመቅረቴ ፣ የመን ላይ ለያዙኝ የወያኔ ደህንነቶች ምስጋና ይግባቸው >>እንዳለ ነግረውናል ።
በነገራችን ላይ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ የጻፉት መጽሐፍ ለገበያ ሲቀርብ << በሀገሪቱ ፈጣን እድገት እንደተገረሙ ፣ በእስር ቤት ውስጥ ይህንን መጽሐፍ ጽፈው ለህትመት እስካበቁበት ድረስ እየተደረገላቸው ስላለው እንክብካቤ ፣ የወያኔ ባለስልጣናትን እንግዳ ተቀባይነት ፣ ድሮ ድሮ ስለ ህውሃት ቶርቸር የሰሙት እና እሳቸው የገጠማቸው ፍጹም የተለያየ እንደሆነ ፣ እንኳን ይቅርና ህዝቡ ፣ እሳቸው፣ ( ምንም እንኳ በአሸባሪነት ቢከሰሱም ) ፣ በቀን ሶስቴ እንደሚመገቡ ፣ ይህም አቶ መለስ ዜናዊ ሀገሪቷን የዛሬ ሃያ ዓመት በቀን ሶሥቴ የሚበላ ሕዝብ እንዲኖር አደርጋለሁ ያሉትን ቃላቸውን እንደጠበቁ ፣ ይህም ቃላቸው እስር ቤት << በወያኔኛ ታች ድረስ ወርዶ እየተተገበረ ያለ ስለመሆኑ >> ፣ ውጭ እያሉ የሰሙት እና እሳቸው ከማይታወቀው እስር ቤታቸው ውስጥ ሆነው ያዩት እጅግ እንደሚለያይ ፣ ያቺ አረንጏዴ ቱታቸውን እንኳ በእንክብካቤ ብዛት እንደወፈረች ፣ በቀን ሶሥቴ በላብ እንደምትታጠብ >> ይተርካል ተብሎ ይጠበቃል ። በነገራችን ላይ ግን አቶ መለስ ዜናዊ << ይህ ሕዝብ የዛሬ 20 ዓመት በቀን ሶሥቴ እንዲበላ እናደርጋለን >> ያሉት መከራውን ነው ንፍጡን ? ሀ ና ለ ያለው ማን ነበር ?
ለማንኛውም አንዳርጋቸው ላፕ- ቶፕ ተሰጥቷቸው ፣ ዘና ብለው ነው ያሉት ። ምንም ማሰብ አያስፈልግም !! እንደውም ፣ እንደውም ትንሽ ኮኔክሽን አስቸግሯቸው ስለነበር ፣ የተሻለ ኮኔክሽን ካለ ቼክ እንዲያረጉ፣ ወደ አዳማ ልከናቸዋል። በነገራችን ላይ የጻፉት መጽሐፍ አርስት << ኢትዮጵያ በልማት ጎዳና ስትጏዝ ፣ እኔና ግንቦት ሰባት ይህንን ለማፍረስ ኤርትራ ድረስ >> የሚል ነው አሉ ።
ለነገሩ እንግሊዝ ሀገር እኮ ላፕ- ቶፕ የለም ። በአሁኑ ጊዜ ፣ ይሄ ልማታዊ መንግስታችን ስለሆነ እንጂ ፣ ማን በነጻ ( ሊያውም እንደ አንዳርጋቸው ላለ ለአሸባሪ) ላፕ- ቶፕ ይሰጣል ? ደርግ ቢሆን ኖሮ እኮ ፣ ላፕ-ቶፕ ሳይሆን አፕ -ሳይድ ዳወን ዘቅዝቆ ተርቸር ነበር የሚያደርገው ። እንደ ወያኔ ያለ ቅዱስ ስርዓት ግን ያንን አይደርግም ። በነገራችን ላይ እኔ እስክንድርም ቢሆን << በቢክ እስክርቢቶ ስንጽፍ ነው ሃሳብ የሚመጣልን>> ስላሉ እንጂ ለነሱም ላፕ-ቶፕ ድርጅታችን ኢህአዲግ አዘጋጅቶ ነበር ።
በነገራችን ላይ እህታችን ርዮት አለሙ ለአራት ዓመት በጡት ህመም ስትሰቃይ ፣ ቢያንስ ቢያንስ የበሽታዋን መንስኤ ታውቅ ዘንድ ፣ ለምንድን ነው ላፕ- ቶፕ ያልተሰጣት ? አንዷለም አራጌ ፣ ተመስገን ደሳለኝ ፣ ውብሸት ታየ ፣ አቡበክር ( አቡኪ )ለምንድን ነው አዳማን እንዳያዩ የተደረገው ? <<በብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች >> እኩልነት የሚያምን ስርዓት ፣ በእስረኞች እኩልነት አያምንም ማለት ነው ? ለዚያውም እስረኞቹ ካንድ የክስ ብሔር የመጡ ሆነው ሳለም እንኳ? ማለጠ ፣ ቢያንስ ቢያንስ ፣ እስከምናውቀው << ከሰማነው >> እነዚህ ሰዎች በሽብርተኝነት ተጠርጥረው ነው የታሰሩት ፣ ታዲያ የዚያ ብዙ የተወራለት ሽብር መስራች እና አናት ላፕ-ቶፕ ሲሰጠው ፣ ቢያንስ ቢያንስ ለነ እስክንድር አይ ፖድ ባለመሰጠቱ አዝነናል ። ደሞ ለሞላ ለተረፈ ኮምፕተር ። <<ቢለዩ ቢለዩ አመትም አይቆዩ>> የሚለው አባባል 24 ዓመት ህዝብና ሕዝብ በመለያየት ለኖረ ስርዓት ይሰራ ይሆን ?
ግን ለመሆኑ እንዴት ነው ለአቶ አንዳርጋቸው የሰጣችሁት ላፕ ቶፕ ባትሪው ከ << ሊትየም >> ይሆን የተሰራው ? ወይኔ ለኔ ቢሆን የሰጣችሁኝ ፣ ሲደብረኝ ባትሪውን ገምጬ አዝናናችሁ ነበር ። ምን ያረጋል !
ለማንኛውም ፣ በሚቀጥለው አቶ አንዳርጋቸውን ሰይፉ ፋንታሁን ሾው ላይ እንደምታሳዩን ተስፋ እናደርጋለን ። አዲስ ስለ ጻፉት መጽሐፍ ሲገልጹ ።
አዎ << To secure ourselves against defeat lies in our own hands, but the opportunity of defeating the enemy is provided by the enemy itself >>። << ራሳችንን ከተሸናፊነት ለመጠበቅ የሚያስችለው ነገር በራሳችን እጅ ላይ ያለ ሲሆን ፣ ጠላታችንን ለማሸነፍ የሚያስችለውን ዕድል ግን ራሱ ጠላታችን የሚያመቻቸው ነው >> የሚለው አባባል ፍጹም እውነት ነው ።

No comments:

Post a Comment

wanted officials