Which one you first choose? በቅድሚያ የሚፈልጉት

Thursday, July 14, 2016

ቁም ስቅላችን ያሳየን የኢትዮሮፕያንስ የለየለት ጽንፈኛ አስተሳሰብ! – በዮሴፍ ሙሉጌታ ባባ (ዶ/ር)

kankokunmalimaali@gmail.com
ክፍል 9
Tensaye የጋራ ግንዛቤ በሌለበት ሀገር/አህጉር ውስጥ እውነተኛ የኢኮኖሚና የፖሊቲካ ነፃነት መጎናጸፍ ዘበት ነው። ብሔራዊ መግባባት ላይ መድረስ የሚቻለው የጋራ ግንዛቤ ሲኖር ብቻ ነው። ሌላው ቀርቶ፣ ባለመስማማት መስማማት (agreeing to disagree) የሚቻለው አሁንም የጋራ ግንዛቤ ሲኖር ብቻ ነው። በዘመናዊነት ስም የተዘረጋዉ አውሮፓዊነት ግን፣ በአፊሪካዊያን ወይም በኢትዮጵያዊን ማኅበረሰብና ሊሂቃን ዘንድ የጋራ ግንዛቤ እንዳይኖር እንቅፋት ሆኗል።
አንድን “ነገር” በመገንዘብ ሂዴት ውስጥ የአተያይ እንቆቅልሽ (puzzles of perception) ወይም የአመለካከት ልዩነት መኖሩ የታወቀ ቢሆንም ቅሉ፣ የአውሮፓዊነት መንፈስና ዘረኛ አስተሳሰብ ስር  በሰደደበት ኢትዮጵያና ለሎች የአፊሪካ ሀገሮች ውስጥ ግን፣ የጋራ ግንዛቤ የመፍጠርን የመሰለ አስቸጋር ስራ የለም። ከሁሉ በላይ፣ በሀገራችን ኢትዮጵያ የጋራ ግንዛቤን ለመፍጠርና  ብሔራዊ መግባባት ላይ ለመድረስ እንቅፋት የሚሆነው የኢትሮፕያንስ የለየለት ጽንፈኛ አስተሳሰብ ነው። ለመሆኑ እነዝህ ኢትዮሮፕያንስ ማን ናቸው?
ኢትዮሮፕያንስ በኩረጃ ፍልስፍና የተካኑና የምዕራባዊያን የአስተሳሰብ ዘይቤ ተከትለው ማንነታቸውን የሰለቡ ግለሰቦች ናቸው። በተለይ ምዕራቡ ዓለም ባስታጠቃቸው ርዕዮተ-ዓለም ወይም ጽንሰ-ሐሳብ ላይ ተመስርተው፣ በፍፁም የበታችነት ስሜት የራሳቸውን ማንነት (ቋንቋ፣ ባህል፣ ታሪክ) አብዝቶ የሚጸየፉ ሲሆን፣ በተቃራንው የነጮችን ባህልና ማንነት በለየለት ሁኔታ ያመልካሉ። ኢትዮሮፕያንስ ዘመናዊነትን እንደ ወረደ በመቅዳት፣ ተጨባጩን የሀገሪቱን ሁኔታ ያላገናዘበና የምዕራቡን ዓለም ፖሊቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ብቻ የሚያስጠብቅ ፖሊስዎችን በመተግበር፣ ሀገራችንን ለእጅ-አዙር ቅኝ-ግዛት ዳርጓታል። ዶ/ር መረራ ጉዲና በትክክል እንደታዘበው “ላለፉት መቶ ሃምሣ ዓመታት ነፃ ሀገር ናት በምትባለዋ ኢትዮጵያ ውስጥ የኢትዮጵያ መሪዎች ሥልጣን ላይ ለመውጣት ወይም ሥልጣን ላይ ከወጡ ቦኋላ ተደላድሎ ለመቆየት እንድችሉ የውጭ ኋይሎች ጉልህ ሚና ሲጫወቱ እንደነበር ነው…በሀገራችን ፖሊቲካ ውስጥ የውጭ ጣልቃ ገብነት ቋም ክስተት እየሆነ መምጣቱን በውል መንገዘብ ጠቃም ይመስለኛል።” (ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ የኢትዮጵያ የታሪክ ፈተናዎች እና የሚጋጩ ሕልሞች፤የኢህአዴግ ቆርጦ ቀጥል ፖሊቲካ፣ 2008፣ ገጽ 16፣17)
ኢትዮሮፕያንስ ከአውሮፓዊያን ጠበብት በኮረጁት የታሪክ አጻጻፍ ስልት፣ የአንድን ሕዝብ ታሪክ ሙሉ በሙሉ አዋርደው፣ ውሸትን አውነት በማስመሰል ጽፈው ያስተምራሉ። ይህ ከቅኝ-ገዥዎች የተቀዳ የታሪክ ትንተናና አረዳድ እኛ-እነሱ የሚል የሁለታዊነት (dualism) ጽንሰ-ሓሳብ (‹ሴሜን-ደቡብ›፣ ‹ክርስቲያን-አረመኔ›፣ ‹ባንዳ-ኢትዮጵያዊ›፣ ‹እስላም-ክርስተያን›፣ ‹ሴማዊ-ሻንቅላ› ወዘተ) በመፍጠሩ ምክንያት እስከ ዛሬ ድረስ በአንድነት ኋይሎችና (ultra-right) በብሔርተኞች (ultra-left) መካከል ‹ያላባራ ጦርነት› አስከትለዋል።
በአብዮቱ ጊዜ በብዙ ሊሂቃን ዘንድ የነበረው አንዱ ችግር ‹የኢትዮጵያ ታሪክ›ን የሚተረጉሙበት መንገድ ነበር። በቅርጽና ይዘት የተለያየ ቢሆንም፣ ይህ የታሪክ አረዳድና ልዩነት የመደብና የብሔር ጥያቄን ይዞ ብቅ ብሏል። የ‹ማንነት› ጥያቄን ያመነጨው ኢህአዴግ እንደሆነ የሚሞግቱ ብዙ ሰዎች አሉ። ይህ ትክክል አይደለም። ኢህአዴግ መተቸት ያለበት የ‹ማንነት› ጥያቄን ከመጠን በላይ እንድለጠጥ በማድረጉ ላይ ነው። በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ‹የማንነት ጥያቄን ያመነጨው ኢህአዴግ ነው› ብሎ መሞገት ግን ከምላስ ላይ ጸጉር እንደመንቀል ይቆጠራል። ተወደደም ተጠላ፣ የመደብም ሆነ የብሔር ጥያቄ በነበረበት ኢትዮጵያ ‹ሁለቱም አልነበሩም› ወይም ‹አንዱ ብቻ ነበር› ብሎ መፈላስፍ በተዘዋዋር ‹በግድ እኛን ሁኑ› የሚል አንደምታ አለው። ‹በግድ እኛን ሁኑ› የሚለውና ከምዕራቡ ‹ዓለም› የተቀዳ አስተሳሰብ በኢትዮጵያ ምድርም እንደማይሰራ ነው።
የበለጠ ግልጽ ለማድረግ፣ በ1960ዎቹ የነበረው ትውልድ (‹ያ ትውልድ›)፣ የሀገራችን ባህልና ኅይማኖት ወይም የሕዝቡን ሥነ-ልቡና ግምት ውስጥ ሳያስገባ፣ ዘመናዊነትን ከእነ አሰስ ገሰሱ በመቅዳት በጊዜው አብቦ የነበረውን የኢትዮጵያ አብዮት አስጠልፏል። ‹ያ ትውልድ› ለውጥ ፈላግ የሆነ ማኅበረሰብ መሆኑ ቢገባንም ቅሉ፣ ለዝህ ታሪካዊ ስህተትና የመጠፋፋት ፖሊቲካ ኋላፍነቱን መውሰድ ይኖርበታል። ይህ ግን የብሔር እኩልነትም ሆነ የሀገር እንድነትን ግምት ውስጥ በማስገባት በሰከነ መንፈስ ሁላችንንም በእኩልነት የሚታስተናግድ ‹ድሞክራሲያዊት› ኢትዮጵያን ለመፍጠር በቃላት ሊገለጽ የማይችል ተጋድሎ ያደረጉትን ጥቅት ቆራጥ ግለሰቦችን አይመለከትም። በተቃራኒው፣ በሕዝብ ብሶትና እንባ ለማትረፍ ሲሉ፣ አንድም በኢትዮጵያ አንድነት ስም፣ አልያም በብሔር ፖሊቲካ ስም ተነስተው የምዕራባዊያንን የኢኮኖሚ አጀንዳ በስውር በማስፈጸም  ሀገራችንን ለእጅ-አዙር ቅኝ-ግዛት የዳረጓትን አድርባይና ወሮ-በላ ኢትዮሮፕያን ፖሊትከኞችንና ምሁራንን ይመለከታል።
ኢትዮሮፕያንስ የአብጎዳጅነት ስሜት በመላበስ፣ በሀገራችን ውስጥ ለሚፈጠረው ማንኛውም ፖሊቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ የውጭውን ዓለም መፍትሔ ይሻሉ። የኢትዮጵያዊያን ችግር በኢትዮጵያዊያን ‹ብቻ› መፈታት ሲገባ፣ የሦስተኛ ወገን ጣልቃ-ገብነት ይሻሉ። በዝህ ምክንያት፣ ሀገራዊ ችግሮቻችንን በመደማመጥ፣ በመነጋገርና በመግባባት መፍታት አይፈልጉም። የምዕራቡ ‹ዓለም› ርዮተ-ዓለም ለህልና ባርነት ስለዳረጋቸው፣ የተወሳሰበ ታሪክና የማንነት ስብጥር ላላት ሀገራቸው ኢትዮጵያ አንድ ወጥ አመለካከት ብቻ የሚያሰርጽ አካሄድ ይተገብራሉ። ይህንን የለየለት ጽንፈኛ አመለካከት ከሁለት ወገን ማየት ይቻላል፤-
  • በአንድ በኩል፣ የተለያየ ቋንቋ፣ ባህልና ታሪክ ያለቸውን ሕዝቦች በጉልበት ጨፍልቀው እንድ በማድረግ ‹በግድ እኛን ሁኑ› የሚል ጽንፈኛ አመለካከት ነው። ‹በግድ እኛን ሁኑ› ማለት ሌላ ሳይሆን፣ የራሳችሁን ቋንቋ፣ ባህልና ማንነት ትታቸው የእኛን ማንነት በኋይልና በጉልበት ተቀበሉ ማለት ነው። ይህ አካሄድ ስበዛ አደገኛ ነው። አንድ ቋንቋ፣ አንድ ሀገር፣ አንድ ኅይማኖት የሚለው ተረታ-ተረት ምን ያህል ዋጋ እንዳስከፈለን የኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪክ ህያው ምስክር ነው። እንድህ ዓይነቱ ፍልስፍናዊ አመለካከት ገዳፊነት (reductionism) የሚባል ሲሆን፣የሰው ልጅ ስለ ራሱ ንጽረተ-ዓለም (worldview) ያለውን አመለካከት (ቅድሜ-ግንዛቤ—pre-understanding) ተቀዳሚና (primordial) መሠረታዊ (fundamental) መሆኑን ስለሚዘነጋ፣ ለብዙኅ-እይታ (multi-perspective) ፈጽሞ ቦታ የለውም። ስለዝህ ንጹሕ-ኢትዮጵያዊ ከእኛ በላይ ለአሳር የሚለው ትምክህተኛ አመለካከት (ዶ/ር መረራ ይህንን አመለካከት ያለቸውን ሰዎች ‹የኢትዮጵያዊነት የምስክር ወረቀት (certificate) ሰጭና ከልካይ አድርጎ ራሳቸውን የሾሙ› ይሏቸዋል)፣ የዘውግ ጥያቄን ወደ ጥግ መስመር (ultra-left) ከመውሰድ ውጭ የሚያመጣው ፖሊቲካዊ ፋይዳ የለውም። የሚከተለው ትዝብት ለዝህ ሀሳብ ትክክለኛነት አንዱ ምስክር ነው፤ “የንጉሡ መንግስት የኤርትራን ፌደረሽን በማፍረስ ያገኘው ጀበሃና ሻዕቢያ የተበሉ[sic] ተቃዋሚዎችን ነው። በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ምንም ዓይነት ጥያቄ የሌላቸውን የመጫ ቱለማ የልማት ማኅበር መርዎችንም በማፈን ያገኘው ውሎ አድሮ የኦሮሞ ነፃ አውጭ ግንባር (ኦነግ)ን ነው። ደርግ በተራው፣ በኢትዮጵያ አንድነት ላይ ምንም ዓይነት ጥያቄ የሌለውንና በዋናነት በትግራይ ልሂቃን የሚመራውን ኢህአፓን በማፈን ያገኘው ሕወሐትን ነው። በዘመኑ ይሻላሉ በሚባሉ የኦሮሞ ልሂቃን ጭምር የሚመራውንና በኦሮሞ አካባቢዎች ሰፍ ምና የነበረውን መኢሶንን በማፈን ያገኘው ለየት ያለ ሕልም ያላቸውን የኦሮሞ ብሔርተኞችን ነው።” (ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ገጽ 23)
  • በሌላ በኩል ያለ ጽንፈኝነት የብሔር ጭቆናንን ማዕከል ያደረገ ፖሊቲካዊ አመለካከት ሲሆን፣ “ምንም ዓይነት የጋራ ታሪክ አልነበረንም” የሚል ተረታ-ተረት ነው። ዶ/ር መረራ ይህንን ወገን “ኢትዮጵያ የሚትባል ሀገር ስም በጆሮየ አልሰማም” ወይም “የታሪክ ሂሳብ እንተሳሰብ” የሚሉ ናቸው ይላቸዋል። በመጀመሪያ፣ በምዕራባዊን ድጋፍ የዛሬይቱን ኢትዮጵያዊ መንግስታዊ ግዛት የፈጠሩ አፄ ምንልክ ነበሩ። የታሪክ አጋጣም ሆነና እነሆ እኛም በዝህ ‹ግዛት› ውስጥ ተገኝንተናል። የመጣንበት መንገድ (አንድ የሆንበት) ግን አንድም በስምምነት ሲሆን፣ ሁለትም በጦርነት ነው። በመሐል አድስ አበባና በአኖለ ላይ የቆሙ ሐውልቶች ለዝህ ሕያው ምስክር ናቸው። የታሪክ ምንጮች ሁሉ የተዛቡ እንጅ ፍፁማዊ የማይሆኑበትም ለዝህ ነው። ስለዝህ፣ በአንድ ግለሰብ ወይም ሕዝብ ላይ ፍፁማዊ ስምምነት መፈለግ የሰው ልጅ ‹ሕልውና›ን ከቅጡ አለመረዳትን ያመለክታል። የኢትሮፕያንስ ዋና ችግራቸውም ይኸው ነው። የፀጉር ስንጠቃ ክርክር ውስጥ ሳልገባ ከዝ በፊት የጻፍኩትን ሓሳብ በግልጽና በአጭሩ ላስቀምጥ፡- የማንኛውም ግለሰብ ወይም ሕዝብ ታሪክ ምልካምና መጥፎ ገጽታ አለው። ስለዝህ፣ አንድም ፍጹም እርኩስ፣ አልያም ፍጹም ቅዱስ አድርጎ ማቅረብ የአስተሳሰብ ሽርሙጥና ይባላል። ፍልስፍና ከምዕራባዊያን ‹ዓለም› ለተቀዳ ለእንደዝህ ዓይነት የታሪክ አረዳድና ትንተና ፈጽሞ ቦታ የለውም። ዞረም ቀረ፣ ከ19ኛው ከ/ዘመን መጨረሻ ወድህ የኢትዮጵያ ሕዝቦችን ከሌላው ጊዜ የበለጠ ያስተሳሰራቸውና ያቀራረባቸው ብዙ የታሪክ አጋጣሚዎች ነበሩ፤ አሉምም። በአንድ ‹ግዛት› ውስጥ ያሉ ሕዝቦች ይቅርና፣ ግለሰቦች ሰው በመሆናቸው ብቻ የሚጋሩ ብዙ እሰቶች አሏቸው። ‹የታሪክ ሒሳብ ካልተወራረድን ሞተን እንገኛልን› የሚል ጽንፈኛ አመለካከት ካልተከተልን በስተቀር፣ የኢትዮጵያ ሕዝቦች አሁንም አንድ ላይ ሆኖ ይህንን ሀገር የማይገነቡበት ምንም ምክንያት አይታየኝም። ሌላው ቀርቶ የእኛ ስምምነትና አንድነት ከምስራቅ አፊሪካም አልፎ፣ ለአህጉራችን አስፈላጊና በጣም ወሳኝ ጉዳይ ነው።
ኢትየሮፕያንስ የምዕራቡ ዓለም መጠቀምያ ከሚሆኑ፣ ከእድሜ ልክ እንቅልፋቸው ነቅተው እነኝህን ሁለቱን ጽንፈኛ አመለካከቶች ለምን እንደማያስታርቁ ለእኔ ፈጽሞ ግልጽ አይደለም። በዓሉ ግርማ ይህንን አሳዛኝ ጉዳይ እንድ ሲል በግጥም መልክ ገልጾት ነበር፡-
የአንድ እናት ልጆች
በአስተሳሰብ ተጣልተው
በአመለካከት ተለያይተው
የሚያስተርቅ ጠፍቶ
የእብድ ገላጋይ በዝቶ

   ዛሬም አንዱ ወገን ሌላውን ከመውቀስ ውጭ የጋራ አጀንዳ ቀርጸን፣ ለሀገራችን ፖሊቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ዘላቅ መፍትሔ ማመንጨት ‹አልቻልንም›። ዝለዝህ አንድ ላይ ‹ማልቀስ› እንጅ አንድ ላይ መስራት አልተቻለም!! የኢትዮጵያ ‹ታሪክ› እስከገባኝ ድረስ፣ የሥነ-ልቦና ጥቅም ካልሆነ እንጅ፣ ባለፉት ሥርዓቶች ሆነ በአሁኑ ወክት በኢኮኖም ረገድ አንድ ወገን ብቻ ተጠቃም ነበር ብሎ መፈላሰፍ፣ ለፖሊቲካ ፍጆታ ክልሆነ በስተቀር ከተጨባጩ የኢትዮጵያ ታሪክ ጋር የተገናኘ አይደለም።
   ኢትዮሮፕያንስ ግን በአጉል ተመጻዳቅነት ‹ወዝ-አደር-ላብ-አደር› ‹ሀገር-ሕዝብ› ‹እናሸንፋለን-እነቸንፋለን› ‹ግለሰብ-ቡድን› ‹ግደታ-ነፃነት› ወዘተ የሚሉ ጽንሰ-ሐሳቦችን አንዱ የሌላው ተቃራን አድርጎ ለማቅረብ ሞክሯል። ይህ የፀጉር ስንጠቃ ክርክር ዛሬም ለእኛ ትውልድ ተርፎ የማንነት ግራ መጋባት ውስጥ ከቶናል። ‹ሀገርና-ሕዝብ› ወይም ‹ግለሰብና-ቡድን›  ወይም ‹ግደታና-ነፃነት›  የአንድ ሣንትም ሁለት ገጽታ መሆኑ እየታወቀ፣ ‹ከአንበሳውና ጐፈረው የትኛው ይቀድማል› ብሎ መፈላሰፍ ለተራበው ዜጋችን ዳቦ ይሆናል ብዬ አላስብም።
   በጣም የሚገርመው፣ ‹ያ ትውልድ› የአሁኑን ትውልድ (በተለይ ወጣቶችን) ግለብ አስተሳሰብ ብቻ እንጅ፣ የበሰለና የጤራ እውቀት እንደሌላቸው አድርጎ ለመሳል ይሞክራል። የትኛው ትውልድ ‹እንደ ጉንዳን ከአንገት በላይ እንደሚወፍር› ለታሪክ ልተወውና፣ ‹ያ ትውልድ› እነደዝህ ዓይነት ወቀሳ በእኛ ትውልድ ላይ ለመሰንዘር የሞራል ብቃት እንደሌለው ለማረጋገጥ ይወዳለው። ኢትዮሮፕያንስ ሆይ! ለመሆኑ ምን ዓይነት ሀገር ነው የተረከብናችው? አብዛኞቻችሁ ለሕዝብ ሰቆቃና ስቃይ መፍትሔ ከማፈላለግ ፋንታ፣ ለግል ጥቅማችሁ ሲትሉ አይደለም እንደ የጥሎ ማለፍ ፖሊቲካ ውስጥ የገባችውት? አንድ መንግስት አልፎ በሌላ ሲተካ፣ ማን ነበር ወይም ማን ነው ገንዘብና ስልጣን ፍለጋ የፖሊቲካ ዥዋዥዌ ስጫወት የኖረው? መስታወት ቤት ውስጥ የሚኖር ሰው አስቀድሞ ድንጋይ መወረወር የለበትም።
   አውነት ነው የእኛ ትውልድም (እዝ ላይ የራሴ ‹ድንቁርና› ይቀድማል) የራሱ የለየለት ደካማ ጎን አለው። ይሁን እንጅ፣ የሁላችን ድክመት መቅረፍ የሚንችለው በኢላፍ-ኢላሜ ፍለስፍናዊ ዜደ (የመደማመጥ፣ የመግባባትና የመነጋገር ፍልስፍናዊ ውይይት—Ilaa-fi-Ilaamee philosophic method of enquiry) በማዳበር እንጅ፣ እርስ በርስ በመወቃቀስና በመናናቅ አይደለም። በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የምርምር ተቋማት አንድም ከትምክህተኝነት፣ አልያም ከጠባብነት የጸዱ ባለመሆናቸው፣ ‹ገለልተኛ› ሆኖ የጠራ ጥናት ማካሄድ አስቸጋር የሚሆነው በዝህ ምክንያት ይመስለኛል። ህልናና ሆድ ፈጽሞ መስማማት ስለማይችሉ፣  አንዳንድ ጊዜ በትምህርተ ዓለምም ‹ብቸኛ› መሆን አይከፋም።  
   ስለዝህ፣ እያንዳንዱ ትውልድ እራሱን መመርመር አለበት። የዛሬው ወጣት ስለ አህምሮውና ማንነቱ ሳይሆን ስለ አለባበሱና ስለ መኪና ብቻ ለምን አብዝቶ እንደሚጨነቅ ወይም ስለ ሕዝቡ ሰቆቃና ስቃይ ሳይሆን ስለ ዶላርዝምና ፔንሲዮን አብዝቶ የሚያስቡ የመንግስት ባለሥልጣንናትና የኅይማኖት አባቶች ለምን እንደ አሸን መፍላት እንደቻሉ መመለስ ያለበት የአሁኑ ትውልድ ብቻ ሳይሆን ‹ያ ትውልድም› ጭምር መሆን አለበት!!! ኢትዮሮፕያንስ ከእኛ ትውልድ ጋራ የሚታረቁበት ጊዜ አሁን ይመስለኛል። የውሃ ቀጠነ ክርክር ትተን የሀገሪቱን ተጨባጭ ሁኔታ ያገናዘቤ ዘላቂ የፖሊቲካ መፍትሔ ማፈላለግ ይኖርብናል። ሕዝብን በሃይመኖትና በብሔር እያከፋፈልን ማፋጀት፣ የምዕራቡን ‹ዓለም› ፖሊቲካዊና ኢኮኖሚዊ ጥቅም ከማስጠበቅ ውጭ ለብዙኅኑ ኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያስገኘው ጥቅም ፈጽሞ እንደሌለ መታወቅ ይኖርበታል። በአጠቃላይ በእሳት የመጫወት አባዜ ለሁላችን የሚበጅ አይመስለኝም።
   እዝ ላይ አንድ ጥያቄ ማንሳት የግድ ይላል፤ “በተለያየ ምክንያት ከላይ የተጠቀሱትን ሁለት ጽንፈኛ አመለካከቶች ፈጽሞ ‹ማስታረቅ› የማይፈልጉ ግለሰቦች ሲያጋጥሙንስ?” የሚል ነው። የኢትዮጵያ ፖሊቲካዊ ፍልስፍና በደንብ ያልገባው እንድ ትምክህተኛ ‹ጓደኛዬ› ኦሮሞ መሆኔን አውቆ ኖሮ፣ ከኦሮሞትና ኢትዮጵያዊነት የትኛውን እንደማስቀድም ጠይቆኝ ነበር። በፍልስፍና ዓለም ውስጥ አንድን ጥያቄ በትክክል ሳይረዱ ጥሩንባ መንፋት ስለማይፈቀድ፤ “ለመሆኑ አንድን ሣንትም ቦርሣህ ውስጥ ስትከት ቀድሞ የሚገባ አንባሰው ነው ጐፈረው?” ብዬ ጠየኩት። ጥያቄዬን መመከት አልቻለም። “ዝለዘህ ሁለቱም በቀጥታ ስለሚመለከተኝ ኦሮሞነት ወይም ኢትጵያዊነት ከእኔ በላይ ለአሳር የሚል ጽንፈኛ አመለካከት ዮሴፍ ዘንድ አይሰራም” አልኩት። ወንድሜ ግን ፈጽሞ ልቀበለኝ አልፈለገም። የሣንትሙን አንዱ ገጽታ (ኢትዮጵያዊነትን) ብቻ እንድመለከት ነዘነዘኝ። ‹ማንነት› የሚለውን ነገር የኋላ ኪሴ ውሰጥ የማልከት ከሆነ፣ ንጹሕ-ኢትዮጵያዊ መሆን እንደማልችል አረጋገጠልኝ። እናም ዋለልኝ መኮንን ትዝ አለኝ፤ “ኢትዮጵያዊ ማን ነው?”
   የማንነት ጥያቄ አንፃራዊ ምላሽ ካገኘ ከ25 ዓመታት ቦኋላ፣ ዛሬም የ‹አበበ በሶ በላ›ና የ‹ጫላ ጩቤ ጨበጠ› ፖሊቲካዊ አስተሳሰብ አለመርገቡ ገረመኝ። እና ምን ማድረግ አለብን/ኝ? ‹የአመጽ ቋንቋ የአመጽን ቋንቋ ብቻ ነው የሚረዳ› የሚል ፍልስፍና መፍትሔ ያስገኝ ይሆን? ይህንን ጉዳይ (በሕይወት ካለው) በክፍል 10 ይመለስበታለሁ።
ቸር እንሰንብት!


No comments:

Post a Comment

wanted officials